ከአዲስ አበባ ወደ ክልሎች ሊጓጓዙ የነበሩ መሳሪያዎችን መያዙን የአዲስ አበባ ፖሊስ አስታወቀ
የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን ከጥቅምት 23 እስከ 30 /2012 ሦስት የተለያዩ ቀናት ውስጥ 7 የተለያዩ አይነት የጦር መሳሪያዎች እና 197 መሰል ጥይቶች ከነተጠርጣሪዎች በቁጥጥር ስር ማዋሉን አስታውቋል። ኮሚሽኑ እንዳስታወቀው ጥቅምት23፣ 28 እና 30/2012 ከተለያዩ ሸቀጦች እና ጭነቶች ጋር በማድረግ ሕጋዊ ጭነት በማስመሰል ወደ ክልሎች ለማጓጓዝ ሲሞከር እጅ ከፍንጅ መያዙን ገልጿል። ሕገ ወጥ የጦር መሳሪያዎች በሕብረተሰቡ ጥቆማ በቁጥጥር ስር መዋላቸውን የገለፀው ኮሚሽኑ አሁንም ሕብረተሰቡ አጠራጣሪ ነገሮችን ሲያይ ለፖሊስ ጥቆማ እንዲያደርግ አሳስቧል።