አርብ ግንቦት 4 ቀን 2015 (አዲስ ማለዳ) በ6ኛ ዙር በተመረጡ በሰባት ክፍለ ከተሞች ከትናንት ግንቦት 03/2015 ጀምሮ ባሉ ተከታታይ አምስት ወራት 50 ሺሕ የመሬት ይዞታዎችን የማረጋገጥ ሥራ እንደሚካሄድ የአዲስ አበባ ከተማ የመሬት ይዞታ ምዝገባና መረጃ ኤጀንሲ አስታውቋል፡፡
በዚህም መሠረት ምዝገባው በኮልፌ ቀራኒዮ፣ በቂርቆስ፣ በንፋስ ስልክ ላፍቶ፣በቦሌ፣በአዲስ ከተማ፣ በልደታና በአራዳ ክፍለ ከተሞች ባሉ 50 ቀጠናዎችና 211 ሰፈሮች እንደሚከናወን ተገልጿል።
ይህ የይዞታ ማረጋገጥ እወጃ ከተላለፈ ከ15 ቀናት በኃላ የይዞታ ይረጋገጥልኝ ጥያቄዎች በክፍለ ከተማ ቅ/ጽ/ቤቶች ቀርበው ጥያቄዎቻቸውን ማቅረብ የሚችሉ መሆኑ ተገልጿል፡፡ለመሬት ይዞታ ማረጋገጥ በተመረጡ ቀጠናዎችና ሰፈሮች ሥራው ተጀምሮ እስከሚጠናቀቅ ባሉት አምስት ወራት ውስጥ፤ የመረጃ ልዩነት እንዳይፈጠር ሲባል ምንም ዓይነት የስመ- ንብረት ዝውውር አገልግሎት እንደማይሰጥም ኤጀንሲው አስታውቋል፡፡
ኤጀንሲው በአዋጅ ከተቋቋመ ጀምሮ እስካሁን ድረስ በ5 ዙር 147 ሺህ ይዞታዎችን በካዳስተር ሲስተም መመዝገቡን አስታውቋል።