የደራሼ ፊላ ፌስቲቫል እየተካሄደ ነው

0
932

በደቡብ ክልል ጊዶሌ ከተማ ደራሼ ወረዳ ፊላ ፌስቲቫል ለሦስተኛ ጊዜ በድምቀት እየተካሄደ ነው።
ባለሦስት ኖታ የሆነው ፊላ የተሰኘው የድምፅ ሙዚቃ መሣሪያ በማኅበረሰቡ በተለያየ ወቅት የሚጫወቱት ሲሆን፤ እህል በተሰበሰበበት በዚህ የጥር ወቅትም ያለ እድሜ ልዩነት ማኅበረሰቡ በጋራ የሚጫወተው ነው።

ደራሼ፣ ኩስሜ፣ ሞስዬ እና ማሾሌ የተባሉ ብሔረሰቦች በጋራ በሚኖርበት ደራሼ ወረዳ፤ ፊላ ማኅበረሰቡን ከሚያስተሳስሩ እሴቶች መካከል አንደኛው ነው።
የጊዶሌ ከተማ ከንቲባ በረከት በመድረኩ መክፈቻ ባደረጉት ንግግር፤ ፊላ የአንድነት፤ የመተባበር፣ የደስታና የመተጋገዝ ምልክት እንደሆነ ጠቅሰዋል።

የደራሼ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አመኑ ቦጋለ በበኩላቸው፤ ፊላ የተለያዩ ብሕሮች ያለ ልዩነት የሚጫወቱት፣ በሃይማኖትም ሆነ በብሔር ያለመበላለጥ የሚሰባሰቡበት ነው ብለዋል። እንደዚሁ ሁሉ የተለያዩ ባህሎች ባሏትና ታሪኮች በተመዘገቡባት ደራሼ መዋዕለ ነዋይ ፈሰስ በማድረግ በጋራ ለመሥራት ለሚሹ ሁሉ ግብዣ አቅርበዋል።
አመራሮቹ በዓሉ በወረዳው ብቻ ሳይሆን በአገር አቀፍ ደረጃ እንዲከበር፤ በዓለምም እንዲታወቅ ማስቻል ይገባል፤ ለዛም ጥረት ይደረጋል ብለዋል።

በአባቶች ምርቃትና ከወራት በፊት በሞት የተለየውን ጋዜጠኛ ካሳሁን አሰፋን በማሰብ የጀመረው መርሃ ግብር የፊላ ፌስቲቫልን በሚመለከት የተለያዩ ጥናታዊ ሥራዎች የቀረቡበት ሲሆን፤ የአደባባይ ላይ ደማቅና ውብ ትርዒቶችንም ያካተተ ነው።

መልስ አስቀምጡ

Please enter your comment!
Please enter your name here