በድሬዳዋ ዛሬም አለመረጋጋቱ እንደቀጠለ ነው

0
759

በድሬዳዋ ባለፉት ቀናት ተከስተው የነበሩ አለመረጋጋቶች ዛሬም በማለዳ እንደቀጠሉ የአዲስ ማለዳ ምንጮች ከስፍራው አስታውቀዋል። ቀፊራ፣ ፈረስ መጋላ፣ ሳቢያን እና ደቻቱ በተባሉ የድሬዳዋ ሰፈሮች መንገዶች ተዘግተው ሰው መንቀሳቀስ እንዳልቻሉም ምንጮች ጨምረው ገልፀዋል።

የዓይን እማኞች ለአዲስ ማለዳ እንደተናገሩት ከንጋቱ 12 ሰዓት ላይ የጀመረው መንገድ መዝጋትና ድንጋይ መወርወር በመከላከያ እና በፌደራል ፖሊስ አማካኝነት የድንጋይ ውርወራው ቢቆምም መንገዶች ግን ዝግ መሆናቸውን ለማወቅ ተችሏል። በከተማዋ ያሉ የመንግስትም ሆነ የግል ትምህርት ቤቶች መዘጋታቸው የተጠቀሰ ሲሆን ነዋሪዎችም በስጋት ላይ እንደሚገኙ ታውቋል።

በከተማዋ የሚገኙ የአዲስ ማለዳ ምንጮች እንዳስታወቁት፣ ከቀናት በፊት ወደ ሀረር ከተማ የሚያስገቡት መንገዶች ተዘግተው የነበሩ ሲሆን ከዛሬ ጥቅምት 12/2012 ጀምሮ ደግሞ ከድሬዳዋ ዙሪያ በተለይም ከደንገጎ እና ገንደ ጋራ አካባቢዎች በመኪና ተጭነው የመጡ ወጣቶች ኹከቱን በመፍጠር የከተማዋን ሰለማ ለማወክ እየሰሩ እንደሆነ  ገልፀዋል።

መልስ አስቀምጡ

Please enter your comment!
Please enter your name here