በሰዉ ላይ የደረሰ ጉዳት አለመኖሩም ታውቋል
ዕረቡ መስከረም 11 ቀን 2015 (አዲስ ማለዳ) በቂርቆስ ክፍለ ከተማ ወረዳ አንድ ፍላሚንጎ አካባቢ ዛሬ ሌሊት 8 ሰዓት ከ34 ደቂቃ ላይ በደረሰ የእሳት አደጋ 3 ነጥብ 8 ሚሊየን ብር የሚገመት ንብረት መውደሙን የእሳትና አደጋ ስጋት ሥራ አመራር ኮሚሽን አስታውቋል።
በአደጋዉ ጉዳት የደረሰባቸዉ የኮምፒዉተርና የጽህፈት መሳሪያ እንዲሁም የሸቀጣሸቀጥ መሸጫ አምስት የንግድ ሱቆች መሆናቸውን የኮሚሽኑ የህዝብ ግንኙነት ባለሙያ ንጋቱ ማሞ ለብስራት ሬድዮ ተናግረዋል።
እሳቱን ለመቆጣጠር 1ሰዓት ከ40 ደቂቃ የፈጀ ሲሆን የኤሌክትሪክ ኃይል ባለሞያዎች የኤሌክትሪክ ኃይል ፈጥነዉ ባለማቋረጣቸዉ አደጋዉ ተባብሶ ንብረት ሊያወድም ችሏል ተብሏል።
አደጋዉን ለመቆጣጠር አምስት የእሳት አደጋ ተሽከርካሪ ሰላሳ የአደጋ ጊዜ ሰራተኞች እንዲሁም ሀያ ሺሕ ሊትር ዉሀ ጥቅም ላይ በማዋል መቆጣጠር ተችሏል።
በአደጋዉ በሰዉ ላይ የደረሰ ጉዳት ባይመዘገብም የአደጋው መንስኤ በፖሊስ በመጣራት ላይ እንደሚገኝም ተገልጿል።