የኢትዮጵያ ኤሌከትሪክ አገልግሎት የሲሚንቶ እጥረት የኮንክሪት ምሰሶ ጥገና ፕሮጀክቶችን እያዘገየበት መሆኑን ገልጿል፡፡ ተቋሙ በሀገር ዉስጥ የሚገኙ የትራንስፎርመር አምራቾችም በሙሉ አቅማቸው በመስራት ላይ ባለመሆናቸዉ አገልግሎቱ ተግዳሮት ገጥሞኛል ማለቱ ተጠቅሷል፡፡
በመሆኑም በተከሰተው የሲሚንቶ አቅርቦት ችግር ምክንያት የሚገነቡ የኮንክሪት የኤሌክትሪክ ምሰሶዎች ግንባታ ላይ መጓተት እየፈጠረበት መሆኑን ነው የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት ያስታወቀው።
የአገልግሎቱ የለዉጥ እና መልካም አስተዳደር ዳይሬክተር እሱባለዉ ጤናዉ ገልጸዋል በተባለው መሰረት፤ ችግሩን ለመቅረፍ ከሲሚንቶ አምራች ኩባንያዎች በቀጥታ ምርቱ ቢቀርብም የምርት እጥረቱ በሀገር አቀፍ ደረጃ የሚገነቡ የኮንክሪት ምሶሶ ጥገና ፕሮጀክቶች እንዲዘገዩ ምክንያት በመሆን ላይ ነዉ ተብሏል። አቅርቦቱ ላይም በሚፈለገዉ መጠን እና ጊዜ በቂ የሲሚንቶ ምርት አገልግሎቱ እንደማያገኝም ተጠቅሷል።
በተጨማሪም፤ የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት፤ በሀገር ዉስጥ የሚገኙ የትራንስፎርመር አምራች ኩባንያዎች በተለያዩ ምክንያቶች በሙሉ አቅማቸዉ እየሰሩ ባለመሆኑ እክል ፈጥሮብኛል ማለቱ ተዘግቧል፡፡ ወደ ሀገር ዉስጥ የሚገቡ የጥሬ እቃ እጥረት እና ከውጭ ምንዛሬ ማግኘት ጋር በተያያዙ ችግሮች፤ አምራች ኩባንያዎች ተስፋ መቁረጥ ዉስጥ ገብተዋል ሲሉ የለዉጥ እና መልካም አስተዳደር ዳይሬክተሩ መግለጻቸው ተመላክቷል።
የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት ትራንፎርመሮቹን በሀገር ዉስጥ ማግኘቱ ከዚህ ቀደም ለግዢ ሂደት የሚፈጀብትን ግዜ እንዲቀንስ ማድረጉን ገልጸዋል። ሆኖም አሁን ላይ የሀገርዉስጥ ትራንስፎርመር አምራች ተቋማት በቀጣይነታቸዉ ዙሪያ ፈተና ላይ መሆናቸዉን አቶ እሱባለዉ ጤናዉ ጨምረዉ ተናግረዋል።
ቅጽ 5 ቁጥር 210 ኅዳር 3 2015