ያልተቀረፈው አገር ‹ማጥፊያ› ስትራቴጂ!

0
540

በኢትዮጵያ አሁን ላይ የሚታዩ ችግሮች መነሻዎች የፖለቲካ ሹመኞች ብቻ ሳይሆን ምሁራንንም ይመለከታል የሚሉት ግዛቸው አበበ፣ ሐሰተኛ የትምህርት ማስረጃን ያነሳሉ። በትክክል ሳይማሩ ወረቀትንና ውጤትን በገንዘብ የሚገዙ ሰዎች በጊዜ ሊፈታ የሚገባውን ችግር ባለመፍታታቸው ዛሬ ላይ ደርሰናል ሲሉም ይሞግታሉ። ይህ አገርን የሚያጠፋ ልብ ያልተባለ አካሄድ ነው ሲሉም፤ ይህንን ለማረም በሐሰተኛ የትምህርት ማስረጃ በብዙ የተፈተነችውን ናይጄሪያን አንስተዋል። ለዚህም የናይጄሪያ መንግሥት የወሰደውን እርምጃ አብራርተው፤ በኢትዮጵያም መሰል አካሄዶች ሊወሰዱ ይገባል ሲሉ ያሳስባሉ።

ባለፈው ዓመት ከትግርኛ ዜና ማሰራጫዎች አንዱ አንድን ዜና ለየት ባለ ትኩረት ለሕዝብ አሰምቶ ነበር። ዜናው ናይጄሪያ በሐሰተኛ የትምህርት ማስረጃ ተጀቡና የከረመችን እንዲት ምኒስትሯን ከሥልጣን ማሰናበቷን የሚተርክ ነው። በእርግጥ ይህ ዜና በብዙ የዓለማችን መገናኛ ብዙኀን በሰፊው ተስተጋብቷል። የትግርኛውን ዜና ለየት የሚያደርገው እርግጠኛነት በሞላበት ድምጸት ‘…በእኛ አገር፣ በፌደራል ይሁን በክልል የሽልጣን ቦታወች ላይ፣ በተመሳሳይ መንገድ ምሁራን ተብለው የተኮፈሱ በጣም ብዙ ባለሥልጣናት እንዳሉ ይታወቃል…’ የሚል የማጋለጥ ዳርዳርታ ወይም ማስጠንቀቂያ የሚመስል ዓረፍተ ነገር ጨምሮበት የነበረ መሆኑ ነው።

ዜናው በአንድ በኩል አገሪቱ ችግር ውስጥ ናት የሚል ተቆርቋሪነት የተላበሰ ቢመስልም፣ በሌላ በኩል ግን ‹‹እያንዳንድህ አርፈህ ተቀመጥ፣ ካልሆነ ጉድህን እዘከዝከዋለሁ!›› የሚል ማስጠንቀቂያ ነው ተብሎ ሊወሰድ የሚችል ዓይነት ነበር። ነገሩ ገራሚም አስደንጋጭም ይሆን የነበረው ስርዓቱ ‹ለዘበኝነት የማይመጥኑ› የሚላቸውን እየመለመለ የሚሾም መሆኑን ባይነግረንና ስርዓቱ ትምህርት እንደ ሸቀጥ እንዲቸረቸር ያልፈቀደ መሆኑን ባናውቅ ነበረ…! የጉዳዩ አሳሳቢነት ግን የሚካድ አይደለም።

በዚህ ዓይነት መንገድ ተምረዋል ተብሎ ከ‹ተራ› ሠራተኛነት እስከ አለቅነት የተደረደሩት ሰዎች በፖለቲካዊና አስተዳደራዊ የሥራ ቦታዎች ብቻ ሳይሆን በዝቅተኛና በከፍተኛ የትምህርት ተቋማት፣ በጤና ጥበቃ አገልግሎት መስጫ ቦታዎች፣ በግብርና፣ በምሕንድስና የሥራ ዘርፎች ወዘተ…. ተሰግስገው ከግለሰብ ጀምሮ እስከ ማኅበረሰብ ብሎም በትውልድ ላይ ጊዜያዊና ቋሚ ችግሮች እየፈጠሩ መሆኑ የሚካድ አይደለም፤ እናም በጊዜ አንድ ሊባል ይገባዋል።

እንግዲህ ‹‹ማን ይናገር የነበረ፣ ማን ያርዳ የቀበረ!›› የሚል የቆየ ብሂል አለንና፣ አንኳንስ እንዲህ ተነግሮ ድሮውንም ቢሆን ሕወሐት/ኢሕአዴግ ለ‹ዘበኝነት› የማይበቁ እያለ የሚመርጣቸውን አድርባዮች ትልቅና የተማሩ ለማስመሰል፣ ይስሙላ የምሁርነት ካባ የሚደርብበት ስርዓት አሰናድቶ፣ በትምህርት እና በአገር መጫወት የጀመረው ገና ሥልጣን እንደያዘ መሆኑን ማንም አይስተውም። ስርዓቱ ወሎ እና አዲስ አበባ ውስጥ ግንቦት 20 ብሎ በከፈተው ትምህርት ቤት፣ ታጋዮቹንና ካድሬዎቹን ከአንደኛ እስከ 12 ክፍል ‘በትምህርት መቀለድ’ ቢባል ተሟልቶ ሊገለጽ የማይችል ቁማር እየተጫወተ መኖሩ የአደባባይ ምስጢር ነው።

በእነዚህ ትምህርት ቤቶች ውስጥ መማር እና መፈተን ትርጉማቸውን እስኪያጡ ድረስ ለይስሙላ የሚደረጉ ጉዳዮች እንደነበሩ በእነዚህ ትምህርት ቤቶች ውስጥ በመምህርነት ያገለገሉት ብቻ ሳይሆኑ በአእምሮ ችሎታቸው የሚተማመኑና ወደ ትምህርት ቤቶቹ ጎራ ብለው የነበሩ ካድሬዎችም የሚመሰክሩት ነገር ነው። በትምህርት ቤቶቹ መደበኛ የክፍል ፈተናዎች ብቻ ሳይሆኑ አገር አቀፍ ፈተናዎችም የትምህርት ቤቶቹን ባህል በተከተለ መንገድ እየተሠሩ፣ ካድሬዎቹ ከፍተኛ ውጤት እያመጡ እንዲያልፉ የሚደረጉባቸው ጨዋታዎች መሆናቸው ሊታወቅ ይገባል።

በትምህርት ቤቶቹ የተጀመረው ጨዋታ የሕወሐት/ኢሕአዴግ ቡድን ሆነ ብሎ በከፈተው ሲቪል ሰርቪስ ኮሌጅ ቀጥሎ፣ ካድሬዎች በቀላሉ የምሁርነት ለምድ እንዲደርቡ እንደሚያደርግም የታወቀ ጉዳይ ነው። ቀስ በቀስ ይህን ጨዋታ የግል እና የመንግሥት ኮሌጆች፣ አገር ቤት ቅርንጫፍ የከፈቱም ሆነ በርቀት እናስተምራለን የሚሉና መሠረታቸው አሜሪካና አውሮፓ የሆነ የፈረንጅ የትምህርት ተቋማትም በሰፊው ተሳትፈውበታል። አሁንም እየተሳተፉበት ነው።

የሕወሐት/ኢሕአዴግ የአንድ ወቅት (በመገናኛ ብዙኀን አካባቢ) ባለሥልጣን የነበረው ተስፋዬ ገብረአብ፣ ከመጽሐፍቱ በአንደኛው ላይ አንድ ታሪክ አስነብቦን ነበር። በርካታ የሕወሐት/ኢሕአዴግ ከፍተኛ ባለሥልጣናት እንግሊዝ አገር በሚገኝ አንድ የትምህርት ተቋም ገንዘብ እየተከፈለላቸው በርቀት ይማራሉ። በርቀት ትምህርት ደንብ መሰረት ወረቀት እየተጻፈ ይላካል፤ እየታረመ ይመለሳል። ጥያቄዎች ከእንግሊዝ ይላካሉ፤ መልስ ተሰርቶላቸው ወደ እንግሊዝ ይመለሳሉ። እንዲህ እንዲህ እየተባለ ማርክና ግሬድ ተሰፍሮ ይሰጣል።

የተስፋዬ ገብረአብ ጽሑፍ እንደሚለው፣ አንድ ጊዜ የእንግሊዙ የትምርት ተቋም ለ ገጽ-ለገጽ ትምህርትና ለግምገማ አንዲት ተወካዩን ይልካል። ባለሥልጣናቱም በአንድ ክፍል ከመምህርቷ ጋር ይገናኛሉ። በትምህርቱ መካከል መምህርቷ ወደ እንግሊዝ ከሚላኩት ወረቀቶች ውስጥ በተደጋጋሚ አስደማሚ የሆኑትን የሚልከውን ባለሥልጣን አድንቃ፣ ባለሥልጣኑ ከአስደማሚ እውቀቱ ለሌሎች እንዲያካፍል የሚችልበትን አጋጣሚ ለማመቻቸት አሰበች። እናም ቀድሞ በወረቀት ከሰፈረው ጉዳይ ጋር የሚገናኝ ጥያቄ ለዚያ ከፍተኛ ባለሥልጣን አቀረበችለት። ዐይን ፍጥጥ ጥርስ ግጥጥ ሆነ ምላሹ።

መምህርቷ እሷንና ባልደረቦቿን ያስደመመበትን እውቀቱን ያካፍል ዘንድ በርትታ ወተወተች። ባለሥልጣኑ ‘…እባክሽን ተይኝ! ሌላ ሰው ነው የሠራልኝ…’ ብሏት እርፍ አለ ይላል፤ የሕወሐት/ኢሕአዴግ ስርዓት ቤተኛና ውስጥ አዋቂ የነበረው ተስፋዬ ገብረአብ ታሪኩን ሲደመድመው።

መገናኛ ብዙኀን ባይነግሩንም ኢትዮጵያችን እነዚህን መሰል ታሪኮች ሞልተው እንዲፈሱባት የተፈረደባት አገር መሆኗ የታወቀ ነው። ይህ አሰራር ስርዓቱ ራሱን ለመጠበቅ ብሎ የዘረጋው ይሁን እንጅ ተሰልቶ የማይደረስበት ኪሳራ አገሪቱን ያከናነበ፣ ትውልድን የገደለ፣ አገርን ያቆረቆዘ መሆኑ የሚያጠራጥር አይደለም። መለስ ዜናዊ እስኪሞቱ ድረስ ጨዋታው ቀስ በቀስ እስከ ማስትሬት ዲግሪ መድረሱ፣ የመለስን ሞት ተከትሎ 3ኛ ዲግሪም የዚህ ጨዋታ ተጠቂ እንዲሆን መደረጉን ለማወቅ እርሳቸው ከመሞታቸው በፊት እና በኋላ ‘ዶክተር’ ተብለው መጠራት የጀመሩ ኢሕአዴጋውያን ብዛት በማየት መረዳት ይቻላል።

አሁን አገሪቱ በማዕበል ውስጥ እየተንገላታች የምትጓዝን መርከብ የመሰለችውና ከላይ እስከ ታች ከዚህ መለስ በማይባል ስፋት ዝርክርክነት የሞላበት አስተዳደር የሰፈነባት በአጋጣሚ አይደለም። የችግሮቹ ሁሉ ዋና ምንጭ አገሪቱን ለመምራት ብቃት፣ እውቀትና ችሎታው ብቻ ሳይሆን አገርንና ሕዝብን ለመምራት ሥነ ልቦናዊ እና ሥነ አእምሯዊ ብቃት የሌላቸው ሰዎች በየቦታው በመሰግሰጋቸው ነው።

ወደ ዋናው ጉዳያችን ስንመለስ፣ ላለፉት በርካታ ዓመታት ትምህርት ጥራቱ በጣም የተጓደለ ከመሆን አልፎ በዚህ የትምህርት ስርዓት ያለፉ ሰዎች በተለይም ፖለቲከኞች ከትንሹ እስከ ትልቁ የሥልጣን ቦታ ላይ እንደተኮፈሱ መቀጠላቸው ከትንሹ መንግሥታዊ አገልግሎት አሰጣጥ ስርዓቶች ጀምሮ እስከ አገራዊ ኢኮኖሚ ግንባታውና የቴክኖሎጂ እመርታው ድረስ ዘርፈ ብዙ ችግሮች እንዲጋረጡበት እያደረገ መሆኑ ከሕዝብ የተሰወረ አይደለም። የሰላም መታጣቱ፣ የአቅርቦት ችግሩና የኢኮኖሚ መቃወሱ የእነዚህ ጉድለቶች ውጤቶች ናቸው።

ከአገር አቋራጭ አውራ ጎዳናች እስከ ከተማ ውስጥ መንገዶች ስጋት የሰፈነባቸው መተላለፊያዎች የሆኑት፣ ዩንቨርሲቲዎች የብቀላ በትር የሚመዘዝባቸው ጦር ሜዳዎች የሆኑት መታሰብ የሚገባው ነገር በሰዓቱ ባለመታሰቡና መደረግ የሚገባው ነገር በወቅቱ ባለመደረጉ መሆኑ ግልጽ ነው። ሹመኞቻችን ነገሮችን ሁሉ የሕወሐት/ኢሕአዴግ ባለሟል በነበሩበት ዘመን በለመዱት የማስመሰልና ለሪፖርት የሚመች ድራማ በመሥራቱ ላይ ተጠምደው እየታዩ ነው። የሰላምና የከፍተኛ ትምህርት ሚኒስቴር መሥሪያ ቤቶች፣ በዩንቨርሲቲዎች ውስጥ የሚቀሰቀሱ ግጭቶችን የሚለኩሱ ጉዳዮችን ምንነትና የለኳሾቹን ማንነት አጥንተው የጥንቃቄ እርምጃዎችን ከመውሰድ ይልቅ ‘የ… ከተማ ነዋሪዎች ለዩንቨርሲቲ ተማሪዎች አቀባበል አደረጉ፣ የ…… ዩንቨርሲቲ አስተዳደር ከከተማው ሕዝብ ጋር የሰላም ኮንፈረንስ አካሄደ፣ በኮንፈረንሱ ላይ ስለ ሰላም አስፈላጊነት የሚሰብክ ግጥም ተነበበ.…’ ወዘተ የሚሉ እንቶ ፈንቶዎችን እየፈተፈቱ ጊዜአቸውን አባክነው ለብዙዎች ሞትና አካል መጉደል ሰበብ ሆነዋል።

ወደ 35 ሺሕ ተማሪዎች መብታቸው ከሆነው የትምህርት ገበታ ርቀዋል፣ ከእነዚህ ውስጥ ጥቂት የማይባሉት ገንዘብ ከፍለው ለመማር ባለመቻላቸው ብቻ ወርቃማ ጊዜቸውን ብቻ ሳይሆን በኃይል የተሞላ የወጣትነት ጊዜአቸውን በከንቱ እያባከኑት ነው። ችግሩ ማቆሚያ ያለው አይመስልም። በማሰፈራራትና በጉልበት በየግቢው ውስጥ የተያዙት ተማሪዎች በተለምዶ የገና እረፍት በሚባለው የእረፍት ጊዜ ወደየ ቤተሰቦቻቸው የሚሄዱ ስንቶቹ ወደ ዩንቨርሲቲ እንደሚመለሱ፣ የስንቶቹ ወላጆች ልጆቻቸው ወደ ዩንቨርስቲዎች እንዲመለሱ እንደሚፈቅዱ በቅርቡ የሚታይ ይሆናል። ይህ ሁሉ የሚሆነው ፖለቲካዊ ሹመኞቻችን ብቻ ሳይሆን ምሁራን ተብለው ዩንቨርስቲዎችን የሚመሩ ግለሰቦችም አእምሯዊና ስለ ልቦናዊ ብቃት ስለሚጎድላቸው መሆኑ ግልጽ ሊሆን ይገባዋል።

ሁሉም ሹመኞች ጠቅላይ ሚኒስትሩ ‹ትምህርቱ ጦር የጦር ሜዳ በሚመስል ሁኔታ ውስጥም ቢሆን ባለበት ይቀጥል› እስካሉ ድረስ በዚሁ መስመር እየነጎዱ ነው፣ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ዛቻቸውን ተከትሎ ‘ዩንቨርስቲዎችን ይዘጉ’ ካሉም ሹመኞቹ ትምህርት ይዘጋ እያሉ እየዘመሩ በዚያው ይመርሻሉ። ከሚኒስትሮች እስከ ዩንቨርሲቲ ዲኖች በዚህ መንገድ እየተግተለተሉ ነው። ሹመታቸው የሚጸናውም እንዲህ ዓይነት ታዛዦች ሆነው እስከቀጠሉ ድረስ ብቻ ነው። ሹመታቸውን ንቀው ለወገኖቻቸው አሳቢ ሆነው፣ ቆም ብሎ ለመነጋገርና ሞጋች ለመሆን የስንት ምስኪን ተማሪ አስከሬን መቁጠር እንዳለባቸው ደግሞ አይታወቅም።

በ1993 አፈንጋጮች ተብለው ሹመታቸውን ከተነጠቁትና ከኢሕአዴጋዊነት ከተባረሩት ሰዎች አንዱ እንደ ሌሎቹ የተባረሩ ጓዶቹ ሌላ የፖለቲካ ድርጅትን ይቀላቀል እንደሆነ ሲጠየቅ ‘….ተመልሼ ኢሕአዴግን በዘበኝነትም ቢሆን አገለግለዋለሁ እንጅ የትም አልሄድም…’ ብሎ ተናግሮ ነበር። ይህ ግለሰብ ከምርኮኛ ወታደሮች መካከል በሕወሐት ተመርጦ ኦሕዴድ የሚባል ፓርቲ እንዲመሠረቱ፣ በተለያዩ ከፍተኛ የሥልጣን ቦታዎች እንዲቀመጡ ከተደረጉት ግለሰቦች መካከል አንዱ ነው። እውነትም የት ይሄዳል? ብዙዎቹም እንዲሁ ናቸው። ወንዝ የማያሻግር ‘ወረቀት’ የት ያደርሳል?
እውቀቱ፣ ብቃቱ፣ ተሞክሮውና መማር የሚፈጥረው የሥነ ልቦና ዝግጁነቱ ሳይኖራቸው ‹ምሁር› ተብለው ሕዝብን (አገርን) እና ከትንንሽ እስከ ታላላቅ መሥሪያ ቤቶች የሚመሩ ‘ፎርጅድ ምሁራን’ መመንጠረ አለባቸው። ይህን አሳሳቢ ችግር ለራስ ይሁን ለሌላው ወገን ብሎ በይሉኝታ ወይም በቸልታ ማለፍ ተገቢ አይደለም። አገርን እያወደሙ ራስን ጠቅሞና ክቦ ለመኖር ከማሰብ የተለየ አይደለም፤ ስስታምነትና ራስ ወዳድነት የተጠናወተው ከፍተኛ ወንጀል ነው። ኢትዮጵያችን ሊቀረፉላት ከሚገባቸው አሳሳቢ ችግሮች አንዱ ይህ ነው።

ይህ በሐሰተኛ ምሁራን የመወረር ችግር የብዙ አፍሪካ አገራት ችግር ቢሆንም የትኛውም የአፍሪካ አገር በመንግሥት ወይም በገዥ የፖለቲካ ቡድን ዕውቅና በዘመቻ መልክ ወይም በይፋ፣ ይህን መሰል ሐሰተኛ ምሁራንን እያራቡ በየቦታው በመሰግሰግ፣ ሕሊና ቢሶችንና አድርባዮችን በየሥልጣን መዋቅሩ በማስቀመጥ የአገዛዝ ዕድሜን ማራዘም አልተካሄደም። በሌሎቹ የአፍሪካ አገራት ላይ ሐሰተኛ ምሁራንን እየፈለፈሉ የሚለቁባቸው፣ የለብ-ለብ ትምህርት እና ፎርጅድ የትምህርት ማስረጃዎችን የሚሸጡ የውጭ የትምህርት ተቋማት ወይም በዚህ ሥራ የተሰማሩ የውጭ ደላሎች ናቸው።

ኢትዮጵያችን ግን የአገር ውስጥ የትምህርት ተቋማትም ጥራቱን ያልጠበቀና ወደ ንግድ ያዘነበለ የትምህርት ስርዓት በመዘርጋቱ ጭምር ነው፣ ሐሰተኛ ምሁራን እንደ አሸን እንዲፈሉባት የተደረገችው።
በዚህ ረገድ ማንም ሰው ሊስተው የማይገባው ነገር የዚህ ዓይነት ትምህርትን ርካሽ ሸቀጥ የማድረጉ ጉዳይ ሲወሳ ስለ ግል የትምህርት ተቋማት ብቻ እየተወራ አለመሆኑን ነው። ጥሩ የመንግሥት ተቋማት እንዳሉት ሁሉ የግል ሆነውም ለመቀለድና በትምህርት ለመሸቀጥ ቦታ የማይሰጡ የትምህርት ተቋማት አሉ። ጊዜዬንና ገንዘቤን መከስከሴ ካልቀረ ተገቢውን ዕውቀትና ሙያ ማግኘት አለብኝ ብሎ በራሱ የሚጥር ካልሆነ፣ ቀልዶ የመመረቁ ጉዳይ በግል ብቻ ሳይሆን በመንግሥት ተቋማትም ሊከሰት ይችላል። ፕሮፌሰርር አስራት ወልደየስን ጨምሮ ወደ 42 ምሁራኑን ብቃት የላችሁም ብሎ ከሥራ ያሰናበተው አዲስ አበባ ዩንቨርሲቲም፣ ከቀልደኞቹ መካከል የሚመደብ መሆኑን መርሳት አይገባም።

እስከ 2010 መገባደጃ ድረስ የፖለቲካ ጉዳዮች ማስፈጸሚያ (የውንብድና) ካምፕ ሆኖ በመቆየቱ ከሥራ ያባረራቸውንና የሚገባቸውን የትምህርት ማዕረግ በፖለቲካዊ መመዘኛዎቹ ከልክሏቸው የነበሩትን መረራ ጉዲናን (ዶ/ር) ዘግይቶም ቢሆን ለሚገባቸው የትምህርት ማዕረግ ያበቃቸውንና ፕሮፌሰር ያደረጋው አዲስ አበባ ዩንቨርሲቲ በፖለቲካዊ ተሳትፎና በፖለቲካዊ ታማኝነት እየመዘነ ዶክተርነትና ረዳት ፕሮፌሰርነት ላለመስጠቱ ምን ምረጋገጫ አለ? ዩንቨርሲቲው ለውጡን ተከትሎ በመረራ ላይ የሰነዘረውን ቅጣት መሰረዙ አገርና ትውልድ ገዳይ ስህተቱን ማረም መጀመሩን እያሳየን ይሆን?

በአሁኑ ሰዓት፣ ብዙዎቹ የአፍሪካ አገራት ሐሰተኛ ምሁራን እግር በእግር እየተከታተሉ መመንጠር፣ አጠራጣሪ በሆነ መንገድ 2ኛ እና 3ኛ ዲግሪ ይዘው የተገኙ ተራ ዜጎችንና ባለሥልጣንትን ጉዳይ ጠለቅ ብሎ ማጣራትና ተምረንበታል የሚሉትን ተቋም ወይም ከዚያ ተቋም የተገኘን የትምህርት ማስረጃ ሐቀኝነት ማጣራቱን ጭምር ጊዜ ሊሰጡት የማይገባ ጉዳያቸው አድርገውታል። በዚህ ረገድ ናይጄሪያ፣ ኬንያና ታንዛንያ ግንባር ቀደም ሆነዋል። እነዚህ አገራት ከከፍተኛ የሥልጣን ቦታዎች ተራ እስከሚባሉት የመንግሥት የሥራ መደቦች ላይ መጠነ ሰፊ ትኩረታቸውን አሳርፈው አገርንና ወገንን የማዳን ኃላፊነታቸውን እየተወጡ ነው። በአገራቸው በትምህርት ማስረጃ የተከለለ ሕገ-ወጥነት እንዳይነግሥም በርትተው እየሠሩ ነው።

ሐሰተኛ የትምህርት ማስረጃን በሚመለከት፣ የትግራይ ዜና ማሰራጫዎች አፍ ማሟሻ የሆነችው ናይጄሪያ፣ ትምህርት ነክ ወንጀሎችን የሚከታተልና የሚያጣራ የደኅንነት ክንፍ፣ ይህን የሚከታተል የእንደራሴዎች ቡድን እስከ ማቋቋም የደረሰ ከፍተኛ ዘመቻ መክፈቷ በአሳሳቢ ደረጃ በችግሩ ውስጥ ለተዘፈቀችው ለኢትዮጵያችንም ትምህርት ሊሆናት ይገባል።

በዚህ ዓይነት ጠንካራ ዘመቻዋን የጀመረችው ናይጄሪያ፣ የአቪየሽን ሚኒስትር የነበረችው የስቴላ ኦዱን ከአሜሪካው ቅዱስ ጳውሎስ ኮሌጅ ተገኘ የተባለ ማስተርስ ዲግሪ እና የት እንዳለ ከማይታወቅ ተቋም አገኘሁት ያለችውን የክብር ዶክትሬት ዲግሪ፣ የፋይናንስ ሚኒስትር የነበረችው የኬሚ አዶሰንን ከኒውዮርክ ሳይንስ ኮሌጅ ተገኘ የተባለ ሰርተፍኬትና የአገራዊ አገልግሎት ምስክር ወረቀት፣ የእንደራሴ ፎስተር ኦጎላ ሕገ-ወጥ መሆኑ ተረጋግጦ ከተዘጋው ጂ.ኤም.ኤፍ ክርስቲያን ዩንቨርሲቲ ተገኘ የተባለ ዶክትሬት ዲግሪ ሐሰተኛ መሆኑ ተደርሶባቸው ለስረዛ የተዳረጉ ሲሆን፣ ኹለቱ ሚኒስትሮች ከሥልጣናቸው ተሰናብተዋል።

ሳሊሱ ቡሀሪ በአንድ ወቅት የናይጄሪያ የታችኛው ምክር ቤት ቃል አቀባይ ነበሩ። ቡሀሪ ካናዳ ውስጥ ከሚገኘው ቶሮንቶ ዩንቨርሲቲ የተመረቁ መሆኑን የሚያሳይ የትምህርት መስረጃ አቅርበው ለሥልጣን የበቁ ሰው ናቸው። የናይጄሪያ መንግሥት በደረሰው ጥቆማ መሰረት በቡሀሪ ላይ ምርመራ መካሄድ መጀመሩን ተከትሎ፣ ቶሮንቶ ዩንቨርስቲ ግለሰቡ ለአንድም ቀን የዩንቨርሲቲው ተማሪ ሆነው እንደማያውቁ በማሳወቁ ቡሀሪ ውርደት ተከናንበው ምርመራው ተዘግቷል።

የወቅቱ ናይጄሪያ ፕሬዘደንት ሙሐመዱ ቡሀሪና የቀድሞው ፕሬዘደንት ጉድላክ ጆናታንም በዚሁ ጉድፍ የተበከሉ ስለመሆናቸው ውዝግብ መቀስቀሱ የታወቀ ጉዳይ ነው። የኹለቱ የናይጄሪያ ከፍተኛ ባለሥልጣናት ጉዳይ አሁንም አከራካሪ ሆኖ እንደ ቀጠለ ነው።

ከአምስት ወራት በፊት ለንደን ላይ በተካሄደ የመጽሐፍት ምረቃ ስነ-ስርዓት ላይ ለተገኙት ለቀድሞው የናይጄሪያ መሪ ሙሐመዱ ቡሀሪ ጦሩን ሲቀላቀሉ ያቀረቡት የ2ኛ ደረጃ ትምህርት ሰርተፍኬት የተጭበረበረ ነው የሚለውን ጉዳይ አስመልክቶ ጥያቄ ቀርቦላቸዋል። እርሳቸው ሲመልሱ ጠቅለል አድርገው ‘… የኹለተኛ ደረጃ ትምህርት ሰርተፍኬት ሳይኖረው በናይጄሪያ ጦር ውስጥ የሚሠራ መኮነን የለም…’ በማለት ነበር። ተባብረው የሚወነጅሏቸውና ሥልጣን እንዲለቁ ግፊት የሚያደርጉባቸው የናይጄሪያ ተቃዋሚ ቡድኖች ‘….አለ የሚባለው የ2ኛ ደረጃ ትምህርት ምስክር ወረቀት ይቅረብና ይመርመር…’ ብለው ቢጠይቁም ቡሀሪ ምስክር ወረቀቱ በእጃቸው እንደሌለ፣ ድንገት በጦሩ እጅ ሊኖር እንደሚችል መልስ ሰጥተው ነበር።

ነገር ግን የናይጀሪያ ጦር የሕዝብ ግንኙነት ዳይሬክተር ብራጋዲየር ጄኔራል ኦላጀዴ ላሊዬ ‘..የሜጄር ጄኔራል ሙሐመዱ ቡሐሪ ሰርተፍኬት ዋና ቅጅ በጦሩ ዘንድ የለም…’ ብለው መግለጫ መስጠታቸውን ደይሊ ኒውስ የተባለ መገናኛ ብዙኀን ገልጿል። ውዝግቡም ቀጥሏል።

ቡሀሪ ፈረንሳይ ስትራስቡርግ በተካሄደው በአውሮፓ ኅብረት ስብሰባ ወቅት (በፈረንጆች አቆጣጠር የካቲት 3/2016) ‘…አገሬን ለማገልገል ባለኝ የጋለ ስሜት ተገፋፍቼ ስህተት ፈጽሜአለሁ…’ ካሉ በኋላ የናይጄሪያን ሕዝብና መንግሥት፣ ቤተሰቦቻቸውንና ጓደኞቻቸውን ይቅርታ ጠይቀዋል የሚል ዜና ተሰራጨ። ሆኖም ብዙም ሳይቆይ የናይጄሪያ መንግሥት በወቅቱ አደረጉት የተባለውን ንግግር ግልባጭ በመገናኛ ብዙኅን በማሰራጨት የፈጠራ ወሬ ነው ሲል አስተባብሏል። ቡሀሪም ይህን መሰሉን ወሬ የሚረጩት አፍሪካን የሚጠሉ፣ ጥቁር ሕዝብን የሚጠሉ… ወዘተ በማለት አፍን ለማዘጋት የሚዳዳው ንግግር ያሰሙበት ወቅት ነበር። መፍትሔው ግን ይህ አይደለም፤ በእርግጥ ‘አገሬን ለማገልገል ያለኝ የጋለ ፍላጎት አሳሳተኝ’ የሚለው አባባል ከአንደበታቸው ወጥቶ ከሆነው ንግግራቸው የመጸጸት ሳይሆን የራስን አጠያያቂ ባህሪ ለመሸፋፈንና ወንጀልን አሳንሶ ለማሳየት ጥቅም ላይ የዋለ አባባል መሆኑ ሊካድ አይገባውም።

‘ጅብ በቀደደው ውሻ ይገባል’ እንዲሉ ሌሎች የናይጄሪያ ፖለቲከኞችም በተመሳሳይ ወንጀል ውስጥ ተዘፍቀው ተገኝተዋል። ይህንንም ‘ዘ ኔት’ (The Net) የተባለ የናይጄሪያ የዜና አውታር በሰፊው ዘግቦታል።

የናይጀሪያ መንግሥት ይህን መሰሉን በትምህርት ማስረጃ ላይ የሚሠራ ቁማር እንደወረርሽኝ በሽታ ቆጥሮ ከፍተኛ ዘመቻ ለማካሄድ የገፋፋው ሌላ ምክንያትም አለ። ይህም በአገሪቱ የሚካሄደውን ቁማር የተረዱ የሌሎች አገራት የትምህርት ተቋማት እንደ ‘አዋጭ ቢዝነስ’ አድርገው በመቁጠር ንግዱ ውስጥ መዘፈቃቸው ነው። ገንዘብ ላቀረበላቸው ናይጄሪያዊ ሁሉ የፈለገው ዓይነት ዲግሪ፣ ከሚመኘው ግሬድና ‘ክብር’ ጋር ያቀርቡለታል። ናይጄሪያውን ለአገራቸው ካላሰቡ ሌላው ስለናይጄሪያ ምን አገባው!

እናም የናይጄሪያ ባካሄደው ዘመቻ፣ በትምህርት ሚኒስትሩ በኩል በዚህ የንግድ መስመር ውስጥ በመሳተፍ የጠረጠራቸውን በርካታ የቤኒን፣ የቶጎ፣ የጋና እና የካሜሩን የትምህርት ተቋማት ጥቁር መዝገብ ላይ አስፍሯል። ከእነዚህና ከሌሎች ተጠርጣሪ ተቋማት የተገኙ ወደ 40 ሺሕ ዲግሪዎችን አግዶ፣ የዲግሪዎቹ ባለቤቶች በሆኑት ናይጄሪያውያን ላይ ምርመራ የሚያካሂድ 16 ሰዎችን ያቀፈ ኮሚቴ ማዋቀሩንም ‘ደይሊ ናይጀሪያን’ የተሰኘ መገናኛ ብዙኀን ዘግቧል።

ናይጀሪያ ችግሩን እንደ ቀላል ጉዳይ አለማየቷ ለብዙ አገራት ትምህርት የሚሆን ነው። የናይጄሪያን ያህል ባይሆንም በታንዛንያም ተመሳሳይ ችግር አለ። ጉዳዩ ያሳሰባቸውና ያበሳጫቸው የታንዛንያ ፕሬዘደንት መሥሪያ ቤቶች እንዲታሰሱ ካደረጉ በኋላ በሐሰተኛ የትምህርት ማስረጃ ሥራ የተቀጠሩ ከዐስር ሺሕ የማያንሱ ሰዎች ከሥራ እንዲባረሩና በነሱ ምትክ በትክክለኛ መንገድ የተማሩ ሰዎች እንዲቀጠሩ አድርገዋል።

ኬንያ አንድን ሐኪም፣ ሕንደ አንድ ሚኒስትሯን ሐሰተኛ የትምህርት ማስረጃ ስለተገኘባቸው ለእስር ዳርገዋል። የሴራሊዮን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሳሙራ ካማራ፣ ለአፍሪካ ልማት ባንክ ፕሬዘደንትነት ሲወዳደሩ ያቀረቡት፣ ከዩናይትድ ኪንግደሙ ሀል ዩንቨርሲቲ ተገኘ የተባለ የፍልስፍና ፒኤችዲ ትክክለኛ ስለመሆኑ ማረጋገጫ የለም በሚል ከውድድሩ ውጭ መደረጋቸው ከተነገረ ኹለት ዓመት ደፍኗል። የኢትዮጵያችን ጓዳስ መቼ ይሆን የሚበረበረው?

የናይጀሪያንና የታንዛንያን ዘመቻ በኢትዮጵያም መድገሙ ለነገ ሊባል የማይገባው ጉዳይ ነው። ጥያቄው ‘ማን በማን ላይ ዘመቻ ያውጅ?’ ሆኖ መፋጠጥ እንዳይኖር መስጋት ተገቢ ነው። ኢትዮጵያችን ከዚህ መለስ ያልተባለ ሥልጣን የተሰጠው መርማሪና አጣሪ ካልተቋቋመላት፣ ነገሩ ሁሉ ‘ከእናንተ መካከል ኃጢያተኛ ያልሆነ ድንጋይ አንስቶ ይውገራት አለ… ያኔ ሁሉም ፈርተው አፈገፈጉ’ እንደሚለው የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ ይገጥማታል። ቢሆንም ከእለታት አንድ ቀን፣ አገርን ለማዳን ሲባል የናይጄሪያን መራር ጽዋ ለመጎንጨት መዘጋጀት ተገቢ ነው።
ግዛቸው አበበ በኢሜል አድራሻቸው
gizachewabe@gmail.com ሊገኙ ይችላሉ።

ቅጽ 2 ቁጥር 66 ጥር 30 2012

መልስ አስቀምጡ

Please enter your comment!
Please enter your name here