የአማራ ክልል ምክር ቤት ዛሬ የካቲት 10/2012 ባደረገው አስቸኳይ ጉዳዔ ላይ የክልሉን ምክትል ርእሰ መስተዳድር ላቀ አያሌው እና የአማራ ክልል የብልጽግና ፓርቲ ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ ዮሐንስ ቧያለው ከስልጣናቸው መነሳታቸው ተቃውሞ አስነሳ ፡፡
ለምክትል ርእሰ መስተዳድር በእጩነት በቀረቡት ፈንታ ማንደፍሮ (ዶ/ር) ላይ የተቃውሞ ሐሳብ ባይቀርብም ክልሉን በለቀቁ መሪዎች ላይ ግን የምክር ቤት አባላቱ ‹‹ክልሉን ለቅቀው ወደ ፌዴራል የሄዱት አራቱም መሪዎች ለክልሉ በሚያስፈልጉበት ወቅት ላይ እንዲነሱ መደረጉ አግባብ አይደለም፡፡ በዚህ ሰዓት ክልሉን ማደራጀት እና እንዲጠናከር በማድረግ ፋንታ ወደ ፌደራል መላክ ክልሉን የአመራርነት መለማመጃ ከማድረግ የዘለለ ትርጉም የለውም›› ብለዋል፡፡
መላኩ አለበል የፌዴራል ሹመታቸው ቀድሞ በፓርላማ የፀደቀ በመሆኑ እና ዮሐንስ ቧያለውም የፓርቲ ተልዕኮ እንጂ ጉዳዩ በምክር ቤቱ የማይታይ ባለመሆኑ እንዲሁም በላቀ አያሌው እና ፈንታ ደጀን ክልሉን መልቀቅ ላይ ምክር ቤቱ የተወያየበት ሲሆን የክልሉ ርእሰ መሥተዳድር ተመሥገን ጥሩነህ የሰው ኃይል ስምሪቱ የፓርቲያቸው መሆኑን ገልጸዋል፡፡
ሹመቱን የማጽደቅና አለማፅደቅ ስልጣን የምክር ቤቱ ነው፤ የምክር ቤቱን ውሳኔ አከብራለሁ ነገር ግን የሌሎች አካላት ተፅዕኖ እንዳለበት ተደርጎ መወሰድ የለበትም ሲሉም ማላሽ መስጠታቸውን አብመድ ዘግቧል፡፡