በምሥራቅ ወለጋ ሊሙ ወረዳ ስምንት ሰዎች በታጠቁ ኃይሎች ተገደሉ

0
950

በኦሮሚያ ክልል ምሥራቅ ወለጋ ሊሙ ወረዳ ስምንት ሰዎች ማንነታቸው ባልታወቀ የታጠቁ ኃይሎች በምሽት መገደላቸውን የአካባቢው የዐይን እማኞች ለአዲስ ማለዳ አረጋገጡ።

ግድያው የተፈጸመው በሊሙ ወረዳ አርቁምቢ መንደር ኹለት በተባለ አካባቢ ሲሆን፤ ኅዳር 21/2013 ምሽት ስድስት ሰዓት ላይ ድንገት የተከሰት ግድያ መሆኑን የአካባቢው ነዋሪዎች አረጋግጠዋል። የአካባቢው ነዋሪዎች የግድያ ሁኔታው ሲያሰረዱ “በዕለቱ ከምሽቱ ስድስት ሰዓት ላይ በአርሶ አደር ሰብል የእሳት ቃጠሎ እና ጩኸት ሰማን፣ የአካባቢው አርሶ አደር ቃጠሎው ቤተክርስቲያን አካባቢ ስለነበር ቤተክርስቲያን ተቃጠለ ብሎ ሲወጣ ቀድመው የደረሱትን ስምንት ሰዎች በጥይት ገደሏቸው” ሲሉ ለአዲስ ማለዳ ተናግረዋል።

ድንገት ተፈጠረ በተባለው ቃጠሎ ከቤታቸው የወጡ ስምንት አርሶ አደሮች ከመገደላቸው በተጨማሪ በትንሹ ከአራት በላይ ሰዎች በጥይት ተመተው መቁሰላቸውን ኗሪዎቹ ለአዲስ ማለዳ ጠቁመዋል። ኗሪዎቹ አክለውም በአካባቢው አስተማማኝ ደህንነት አለመኖሩን የጠቆሙ ሲሆን፣ በዚህም ከፍተኛ የደህንነት ስጋት ውስጥ መግባታቸውን ገልጸዋል።

ግድያውን ፈጽመው በምሽት የተሰወሩ አጥቂዎች በአካባቢው በቅርብ ርቀት በሚገኝ ዋጃ ተብሎ በሚጠራ ጫካ ውስጥ መግባታቸውን ኗሪዎቹ ገልጸዋል። አጥቂዎቹን አሳዶ የሚይዝና የአካባቢውን ማኅበረሰብ ሰላም የሚስጠብቅ የጸጥታ አካል ጉዳዩን ለአዲስ ማለዳ እስካስረዱበት ስዓት ድረስ አለመግባቱን አረጋግጠዋል።
በተፈጠረው ግድያ የተደነጋገጡ የአካባቢው አርሶ አደር ኗሪዎች አካባቢውን ለቀው ለመውጣት መንገድ ላይ የደህንነት ስጋት ስላለብን ወዴት እንደ ምንሔድ ግራ ገብቶን ተጨንቀናል ብለዋል። በአካባቢው የተፈጠረው የደህንነት ስጋት የክልሉ መንግሥት በአስቸኳይ የጸጥታ ኃይል ልኮ አጥፊዎችን ለሕግ እንዳቀርብላቸውና ሰላማቸውን እንዳስጠብቅላቸው ኗሪዎቹ ጠይቀዋል።

በሌላ በኩል ኅዳር 21/2013 ጥቃት ፈጽመው ወደ ዋጃ ጫካ ገብተዋል የተባሉ አጥቂዎች ቁጥራቸው ከ17 በላይ የሚሆኑ አርሶ አደሮችን አግተው ጫካ እነዳስገቧቸው ኗሪዎቹ ጠቁመዋል። ታግተዋል የተባሉት አርሶ አደሮች አዲስ ማለዳ ኗሪዎቹን አስካነጋገረችበት ስዓት ድረስ ያሉበት ሁኔታ እነደማይታወቅ ከኗሪዎች አንደበት ሰምታለች።

ታግተዋል የተባሉትን አርሶ አደሮች ያበትን ሁኔታ የጸጥታ ኃይል በአስቸኳይ ገብቶ እንዲያፈላልግ እና የአካባቢውን ሰላም እንዲጠብቅ ኗሪዎች ቢጠይቁም አስካሁን የተሰጣቸው ምላሽ እንደሌለ ለአዲስ ማለዳ ተናግረዋል። በአካባቢው ያለው የጸጥታ ኃይል አጥቂዎቹን ተከታትሎ እንዲይዝና ታግተዋል የተባሉትን አርሶ አደሮች ተከታትሎ ሕይወታቸውን እንዲታደግ ቢጠይቁም ተከታትለው መያዝ እንዳልተቻለ ተናግረዋል።

የጥቃት ፈጻሚዎቹን ማንነት በተመለከተ አዲስ ማለዳ ለኗሪዎቹ ባቀረበችው ጥያቄ በአንድ በኩል ሌሊት ስድስት ሰዓት ላይ ጥቃት አድርሰው የተሰወሩ አጥቂዎች ማንነታቸወን ማረጋግጥ እንዳልቻሉ የገለጹ ሲሆን፣ በሌላ በኩል ደግሞ ከ17 በላይ አርሶ አደሮችን አግተው ጫካ ወስደዋል ተብለው የሚጠረጠሩት የኦነግ ሸኔ አባላት መሆናቸውን ኗሪዎቹ አረጋግጠዋል።

አዲስ ማለዳ በጉዳዩ ላይ የኦሮሚያ ፖሊስ ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነር የሆኑትን ግርማ ገላንን ጠይቃ በጉዳዩ ላይ ምላሽ እንድሰጡ ብትጠይቅም “ምላሽ አልሰጥም” በማለት እምቢታቸውን በመግለጻቸው አዲስ ማለዳ የነዋሪዎቹን ጥያቄ ከክልሉ ፖሊስ ኮሚሽን ምላሽ ልታገኝ አልቻለችም።

በኦሮሚያ ክልል በተለይም በምስራቅና በምዕራብ ወለጋ አካባቢዎች የኦነግ ሽኔ አባላት መሆናቸው በተደጋጋሚ የሚገለጽላቸው የታጠቁ ኃይሎች በተለያየ ጊዜ በንጹሐን ዜጎች ላይ ግድያ ሲፈጽሙ በተደጋጋሚ የሚሰማ መሆኑ የሚታወስ ነው።

ቅጽ 2 ቁጥር 109 ኅዳር 26 2013

መልስ አስቀምጡ

Please enter your comment!
Please enter your name here