የአማራ ክልል የአደጋ መከላከልና ዝግጁነት ኤጀንሲ እና የምግብ ዋስትና ማስተባበሪያ ቢሮ በክልሉ የሚገኙ ተፋናቃዮችን መልሶ ለማቋቋም 221 ሚሊየን ብር (8 ሚሊየን ዶላር) እንደሚያስፈልገው ገለጸ።
በክልሉ የሚገኙ ተፈናቃዮች እንዴት መረዳት እንዳለባቸው አቅጣጫና ዕቅድ ያስቀመጠው ቢሮው፤ ለተጎጂዎች የምግብ፣ የጤና እና የትምህርት አገልግሎት ለማቅረብ አፋጣኝ ዕርዳታ ያስፈልገኛል ብሏል።
ተጎጂዎቹ በጎንደር፣ ጎጃም፣ ወሎ፣ ሰሜን ሸዋ እና ዋግኽምራ ዞኖች የሚገኙ ሲሆን በአገሪቷ በነበረው አለመረጋጋት የተነሣ ከአፋር፣ ቤኒሻንጉል ጉሙዝ፣ ኦሮሚያ እና ሱማሌ ክልሎች አንዲሁም ከጅቡቲ ከባለፈው ዓመት ግንቦት ወር ጀምሮ ከመኖሪያ ቀያቸው የተፈናቀሉ ናቸው።
የዓለም አቀፍ ስደተኞች ድርጅት መረጃ እንደሚያሳየው እስከ ባለፈው ኅዳር 2011 ድረስ 14 ሺህ የሚሆኑ ተፋናቃዮች በአማራ ክልል ይገኛሉ። በተጨማሪ 320 ተፈናቃዮች ከተለያዩ ቦታዎች በየሳምንቱ ወደ ክልሉ እንደሚገቡ የድርጅቱ መረጃ ያሳያል።
ቅጽ 1 ቁጥር 9 ጥር 4 ቀን 2011