ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በሕገ ወጥ መንገድ ወደ ኢትዮጵያ እየገባ የሚገኘውን ቁጥሩ የበዛ የጦር መሳሪያን ለመቆጣጠር ኢትዮጵያ ከጎረቤቷ ሱዳን ጋር ዲፕሎማሲያዊ ድርድር እያደረገች እንደሆነ ተገለፀ።
በሕገ ወጥ የጦር መሳሪያዎች ጉዳይ የኢትዮጵያ መንግሥት ከሱዳን አቻው ጋር ዲፕሎማሲያዊ ውይይት እያደረገ እንደሆነ እና በቁጥጥር ስር የዋሉ መሳሪያዎች ላይ ምርመራ አካሂዶ እስከ አምራች አገራት ድረስ የዘለቀ ድርድር እያካሄደ እንደሚገኝ ተገልጿል። ይሁን እንጂ አሁንም ድረስ ወደ አገር ውስጥ የሚገባው ሕገ ወጥ መሳሪያ አለመቀነሱንና መንግሥትም ከሱዳን መንግሥት ጋር የሚያደርገው ድርድር እንደቀጠለ መሆኑን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ ነብያት ጌታቸው ሐሙስ የካቲት 6 በሰጡት መግለጫ አስታውቀዋል።
የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ወርቅነህ ገበየሁ (ዶ/ር) ጥር 21/2011 ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የመስሪያ ቤታቸውን የግማሽ ዓመት ሪፖርት ባቀረቡበት ወቅት ወደ አገር ውስጥ የሚገባው ሕገ ወጥ የጦር መሳሪያ በአብዛኛው ከሱዳን በኩል እንደሚገባ መግለፃቸው ይታወሳል።
ከሐምሌ 1/2010 እስከ ታኅሣሥ 30/2011 ባሉት ስድስት ወራት ብቻ ኹለት ሺህ 383 የተለያዩ የጦር መሳሪያዎች በሕገ ወጥ መንገድ ወደ አዲስ አበባ ሲገቡ መያዛቸውን ከአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን የተገኘው መረጃ ያስረዳል።
ቅጽ 1 ቁጥር 14 የካቲት 9 ቀን 2011