2.7 ሚሊዮን የአገር ውስጥ ተፈናቃይ የያዘችው ኢትዮጵያ ለዜጎች መጀመሪያ የዕለት ደራሽ እርዳታ ለማቅረብ ሲያልፍም በዘላቂነት ለማቋቋም የመንግሥት አቅም ብቻ የሚችል ባለመሆኑ ሁሉም እንዲረዳ ጥሪ አቅርባለች። 90 ሺሕ ተፈናቃዮች እንዳሉት ያሳወቀው የአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥትም የእርዳታ ጥሪ በማቅረቡ የተለያዩ ድጋፎች እየተደረጉለት ነው።
መንግሥታዊው ንግድ ባንክ በጥናት ላይ የተመሰረተ ድጋፍ ማድረግ እንደሚፈልግ ከገለፀ በኋላ ድጋፍ ይፈልጋሉ ለተባሉት ኢትዮጵያዊያን በየክልላቸው በኩል እንዲደርሳቸው የ100 ሚሊዮን ብር ደግፏል። ባንኩ 100 ሚሊዮን ብሩን ለክልሎች ሲያከፋልም የተጠቀመው ቀመር የተፈናቃዮቹ ቁጥር ላይ መሰረት ያደረገ መሆኑን አሳውቋል። በዚህም ብዙ ተፈናቃይ ያላቸው ክልሎች ከፍተኛውን ገንዘብ ሲወስዱ የተፈናቃዮች ቁጥር ትንሽ የሆነባቸው ክልሎች ትንሹ መጠን ይደርሳቸዋል።
በዚህም አማራ ክልል ለ90 ሺሕ ተፈናቃዮቹ የሚደርሰው ገንዘብ 4 ሚሊዮን ብር አካባቢ መሆኑ ሲገለፅ ክልሉ (የድጋፍ ሰብሳቢ ኮሚቴው) ንግድ ባንክ ያደረገውን ድጋፍ ቢያከብርም ገንዘቡን እንደማይቀበለው አሳውቋል። ምክንያት ያለው ደግሞ ብሩ የክልሉን ሕዝብ ክብር አይመጥንም የሚል ነው።
ባንኩ ክልሉ ውስጥ ካሉት ቅርንጫፎች ብዛትና ከክልሉ ሕዝብ ከሚያገኘው ገቢ አንፃር ለአማራ ክልል የመደበው ገንዘብ አይመጥንም በሚል ውድቅ መደረጉም ብዙዎችን በማኅበበራዊ መገናኛ ገጾች ሲያከራክር ሰንብቷል። በአንድ በኩል ባንኩ የተፈናቃዮች ቁጥር ላይ መሰረት አድርጎ ያደረገው ክፍፍል ፍትሓዊ ነው የሚለው እና የዚህ ተቃራኒው ሐሳብም በፌስቡክ ገፆች መከራከሪ ሆኖ ቀጥሏል። የክልሉ መንግሥት ሰራተኞችም በንግድ ባንክ በኩል ይከፈላቸው የነበረው ደመወዝ ወደ ሌላ ባንክ እንዲዛወር በመጠየቅ ባንኩን እየተቃወሙ ይገኛሉ።
ቅጽ 1 ቁጥር 21 የመጋቢት 21 ቀን 2011