ህብረት ኢንሹራንስ ኩባንያ በቅርቡ የእሳት አደጋ ለደረሰበት በቢሾፍቱ ለሚገኘው የኢስት አፍሪካ ታይገር ብራንድ ኢንዱስትሪ 24 ነጥብ አንድ ሚሊየን ብር ካሳ መክፈሉን አስታወቀ፡፡ ይህ ኢንሹራንሱ ከፍተኛ ካሳ ከከፈለባቸው አደጋዎች ተርታ የሚመደብ ሲሆን፣ ኢስት አፍሪካ ታይገር ለባለፉት ሁለት ዓመታት የኢንሹራንስ ኩባንያ ደንበኛ ነበር፡፡
የኢስት አፍሪካ ታይገር ብራንድ ሃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማህበር ጥር 24፣ 2011 በሰዎች ላይ ከደረሰው አደጋ በተጨማሪ 50 ሚሊዮን ብር የሚገመት ንብረት እንደወደመበት ይታወሳል፡፡
ህብረት ኢንሹራንስ ከተመሰረተ ሁለት አስርት አመታትን ያስቆጠረ ሲሆን አጠቃላይ ሀብቱ 1.3 ቢሊየን ብር ይደርሳል፡፡ ኩባንያው 473 ሚሊየን አረቦን ባለፈው በጀት አመት የሰበሰበ ሲሆን፣ ያገኘው ትርፍ 108.8 በመቶ እድገት በማሳየት 124.4 ሚሊየን ብር ደርሶ ነበር፡፡
በ2010 የሒሳብ ዓመት መጨረሻ ላይ የሕብረት ኢንሹራንስ አክሲዮን ማኅበር ጠቅላላ የተከፈለ ካፒታል 250 ሚሊዮን ብር ሊደርስ ችሎ ነበር፡፡
ቅጽ 1 ቁጥር 21 የመጋቢት 21 ቀን 2011