በደቡብ ኢትዮጵያ ዲላ ከተማ መንግሥት የጎሳ ግጭት፣ ግድያና መፈናቀልን እንዲያስቆም ለመጠየቅ የአካባቢው ነዋሪዎች ሊያደርጉት የነበረውን ሰልፍ በአካባቢው ባለሥስልጣናት ታገደ።
ከአስተባባሪዎች አንዱ የሆኑት መምህር ክብሩ ማሞ ሰልፉ መንግሥት ዜጎችን ያፈናቀሉ ግለሰቦችና ቡድኖችን በሕግ ለመጠየቀ ቃል ከመግባት የዘለለ ተግባራዊ ርምጃ እንዲወስድ የሚጠይቁ መልዕክቶችን ለማስተጋባት ታስቦ አንደነበር ገልጸዋል።
ኢትዮጵያ ውስጥ ባለፈው አንድ ዓመት በጎሳ ላይ ባነጣጠሩ ጥቃቶች በርካታ ሰዉ ከተገደለና ከተፈናቀለባቸው አካባቢዎች አንዱ የጌዴኦ ዞን ሲሆን ከግማሽ ሚሊዮን በላይ የሚሆን ሕዝብ ተፈናቅሏል። መንግሥት ለተፋናቃዮቹ ድጋፍ እንዲያደርግ እና አፈናቃዮችን ለፍርድ እንዲያቀርብ ተበዳዮችና ለተበዳዮች የሚቆረቆሩ ወገኞች ባደባባይ ሰልፍ ለመጠየቅ በዲላ ተዘጋጅተዉ ነበር። ይደረጋል ተብሎ የነበረዉ ሠልፍ አደራጆች እንደሚሉት፣ የአካባቢዉ ባለሥልጣናት ሠልፉን ከፈቀዱ በኋላ በዋዜማው ምሽት አግድውታል።
አስተባባሪዎቹ ከዲላ ከተማና ከጊዲኦ ዞን አስተዳደር ፍቃድ ማግኘታቸውን ጠቅሰው ሰልፉን ፍፁም ሰላማዊ በሆነ መንገድ ለማከናወን መልዕክቶችን ያዘሉ ካኔቴራዎችና መፈክሮች አዘጋጅተው እንደነበርም ተናግረዋል። ይሁን እንጂ ሕገ መንግሥታዊ መብቱን ተጠቅሞ ጥያቄውን ለማቅረብ በተዘጋጀበትና በርቀት የሚገኙ የሰለፉ ተሳታፊዎች ምሽቱን ወደ ዲላ ከተማ እየገቡ ባሉበት ወቅት ሰልፉን ማካሔድ እንደማይችሉ የሚገልድ ደብዳቤ እንደደረሳቸው አስተባባሪዎቹ ገልጸዋል።
ቅጽ 1 ቁጥር 26 ሚያዚያ 26 ቀን 2011