ብረታ ብረትና ኢንጅነሪንግ ኮርፖሬሽን ከዓመታት በፊት በ108 ሚሊዮን ብር የገዛውን እና ለቢሮ አገልግሎት ሲጠቀምበት የነበረውን የኢምፔሪያል ሆቴልን እንደሚለቅ ፋና ዘግቧል። ሜቴክ 108 ሚሊዮን ብር የገዛውን ሕንፃ በኹለት ወር ጊዜ ውስጥ እንዲለቅ የተደረገው በሽያጭ ሒደቱ ወቅት ለገቢዎች ሚኒስቴር መክፈል የነበረበትን 32 ሚሊዮን ብር ባለመክፈሉ እንደሆነ ተገልጿል።
ሜቴክ ሕንፃውን ከገዛው በኋላ ሕጋዊ የባለቤትነት ሳያሟላ ሕንፃውን ለቢሮ ግልጋሎት እየተጠቀመበት እንደሚገኝ የሚታወቅ ሲሆን ፥ ይህም ሕጋዊነት የሌለው አካሔድ እንደሆነም ለማወቅ ተችሏል። የስም ማዞሩ ሒደት በሙሉ ሊፈፀም ያልተቻለበት ምክንያትም ሕንፃውን ለሜቴክ የሸጠው አካል መጀመሪያውኑ ሕንፃውን ከገዛው አካል ጋር ስም አዙሮ ባለመጨረሱ እንደሆነ ተገልጿል። የገቢዎች ሚኒስቴር በኦዲት ግኝት የታየውን ክፍተት ገዢው አካል ወይም የሕንፃው ባለቤት እንዲከፍለው ቢጠየቅም ከፋይ ማግኘት አልተቻለም።
የገቢዎች ሚኒስቴር ሚኒስትር ደኤታ አቶ ዘመዴ ተፈራ፥ በሽያጩ ወቅት መረጃ ማግኘት ስለማይቻል ሚኒስቴሩ ገንዘቡን መጠየቅ የሚችለው አሁን ላይ የሕንፃው ባለቤት የሆነውን አካል ነው ብለዋል።