ኢትዮጵያ አየር መንገድ ከአውሮፓዊው ግዙፍ የአውሮፕላን አምራች ኩባንያ ኤር ባስ ጋር የ1 ነጥብ 6 ቢሊዮን ዶላር ስምምነት ሊፈራረም መሆኑ ታወቀ። አየር መንገዱ ከኤር ባስ ጋር የሚገባው ውል ኻያ ኤር ባስ ኤ220 ጀት አውሮፕላኖችን ለመግዛት እንደሆነ ለማወቅ ተችሏል።
የኢትዮጵያ አየር መንገድ ከዚህ ቀደም የኤር ባስ ምርቶችን ለመግዛት አቅዶ ሃሳቡን በመቀየር በመጠናቸው ከፍ ያሉ እና ብዙ መንገደኞችን የመጫን አቅም ያላቸውን የቦይንግ ምርት የሆኑትን ቦይንግ 737 ቤተሰብ የሆኑ አውሮፕላኖችን መግዛቱ ተጠቅሷል። ይሁን እንጂ አየር መንገዱ በቅርቡ ከአጋጠመው የአውሮፕላን አደጋ ወዲህ ፊቱን ወደ አውሮፓዊው ኩባንያ መመለሱንና ይህን ያህል ቢሊዮን ዶላሮች ውል ለመፈራረም መወሰኑ እንደምክንያት ተነስቷል። የኢትዮጵያ አየር መንገድ ዋና ስራ አስፈፃሚ ተወልደ ገብረማሪያም ስለ ኤር ባስ ኤ220 አውሮፕላኖች በሰጡት መግለጫ ለረጅም ጊዜያት አየር መንገዱ ጊዜ ወስዶ እንዳጠናቸው እና ተመራጭ ሆነው እንደተገኙም አስታውቀዋል። ስምምነቱ በፈረንጆች 2019 መገባደጃ ላይ እንደሚጠናቀቅ የተገለፀ ሲሆን የኢትዮጵያ አየር መንገድ ከባለፈው ዓመት ካጋጠመው አሰቃቂው የአውሮፕላን አደጋ ወዲህ አውሮፕላኖችን ሲገዛ የመጀመሪያው እንደሚሆንም ታውቋል።