ረቡዕ ኀዳር 14 ቀን 2015 (አዲስ ማለዳ) ራሱን የኦሮሞ ነጻነት ሰራዊት ብሎ የሚጠራውና በመንግሥት “ኦነግ ሸኔ” የሚባለው ታጣቂ ቡድን ባሳለፍነው ሰኞ ኀዳር 12 ቀን 2015 ምሽት ላይ 17 ሰዎችን መተሐራ አካባቢ ማገቱን አዲስ ማለዳ ሰምታለች፡፡
ታጣቂ ቡድኑ እገታውን የፈጸመው ምሽት 12 ሰዓት አካባቢ ሲሆን፤ እገታው የተፈጸመው ከአዳማ ወደ መተሐራ ከተማ ተሳፋሪዎችን ጭኖ በመጓዝ ላይ የነበረ ዶንፊን መኪና ላይ ነው፡፡
አጋቾቹም የመኪናው ሹፌርና ረዳት ጨምሮ የመኪናው ሹፌርና ረዳት ኹሉንም ተሳፋሪዎች ማገታቸው የተገለጸ ሲሆን፤ ሰዎቹ የታገቱበት ቦታም ኦሮሚያ ክልል ምስራቅ ሽዋ ፈንታሌ ወረዳ መተሐራ ከተማ አካባቢ ልዩ ሥሙ አሪቦና የሚባል ቦታ ነው፡፡
ታጣቂ ቡድኑ ሰዎቹን ካገተ በኋላ ተቆጣጠሮ ወደሚገኝበት ጫካ እንደወሰዳቸውም ተነግሯል። ከታገቱት 17 በሰዎች መካከል 13 ወንዶች 4ቱ ደግሞ ሴቶች መሆናቸው ታውቋል። ታጣቂ ቡድኑ ከእገታው በኋላ 4ቱን ሴቶች ምንም አይነት መረጃ እንዳይሰጡ በማስጠንቀቅ እንደለቀቃቸውም ተገልጿል፡፡
በመተሐራ አካባቢ “ኦነግ ሸኔ” ተብሎ የሚጠራው ታጣቁ ቡድን በስፋት እንደሚንቀሳቀስ አዲስ ማለዳ ከአካባቢው ሰዎች ሰምታለች፡፡ የቡድኑን እንቅስቃሴና ጥቃት ለማስቀረት የመከላከለያ ሠራዊት በአካባቢው የተሰማራ ቢሆንም፣ ሠራዊቱ ባልደረሰባቸው አካባቢዎች ቡድኑ የግድያና የእገታ ጥቃቱን እንደቀጠለ መሆኑ ተነግሯል፡፡
የታጣቂ ቡድኑ ግድያ እና ጥቃቶች የብሔር ማንነትን መሰረት የደረገ መሆኑንም የአካባቢው ነዋሪዎች ይገልጻሉ፡፡ የቡድኑ የእለት ከእለት ተግባር ሆኗል የተባለው እገታ፣ ሰዎችን በመሰወር ከቤተሰቦቻቸው ብር የመቀበያ ሰልት ሆኗል ተብሏል፡፡
በአካባቢው ከአንድ ወር በላይ የስልክ አግልግሎት የተቋረጠ ሲሆን፣ አልፎ አልፎ ለስዓታት እንደሚለቀቅ አዲስ ማለዳ ሰምታለች።