በኢትዮጵያ እየተንቀሳቀሱ የየሚገኙት ሁሉም ተፎካካሪ ፓርቲዎች በመጭው ምርጫና የዴሞክራሲ ሒደቱ ላይ ከጠቅላይ ሚንስትሩ ጋር ሊወያየዩ ነው።
የጠቅላይ ሚንስትር ጽሕፈት ቤት እንዳስታወቀው ማክሰኞ፣ ኅዳር 18 በሚካሔደው ውይይት የዴሞክራሲ ስርዓቱን ጅማሮ ማስቀጠል እና የመጭውን ዓመት ምርጫ ነጻና ተአማኒ ማድረግ በሚቻልባቸው ጉዳዮች ላይ ያተኩራሉ።
የሁሉም ፖለቲከ ፓርቲ ሊቀ መናብርት የውይይቱ ተሳታፊ እንዲሆኑ ጥሪ የቀረበ ሲሆን፣ የፖለቲካ ፓርቲዎች ሁሉንም በአገር ውስጥ ተመዝግበው እየተንቀሳቀሱና ከውጭ ጥሪ ተደርጎላቸው የገቡትን ሁሉ ያካትታል።
በማክሰኞው ውይይት መሳተፍ የሚፈልጉ የፖለቲካ ማኅበራት አመራሮች እስከ ሰኞ 11፡00 ሰዐት ድረስ ማመልከት እደሚችሉም ጽሕፈት ቤቱ ባወጣው መግለጫ አመልክቷል።
ጠቅላይ ሚንስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ወደ ሥልጣን ከመጡ ወዲህ በተደጋጋሚ ሲያነሷቸው ከተደመጡት ጉዳዮች መካከል ከተፎካካሪ ፖለቲካ ፓርቲዎች ጋር በቅርበት መሥራት የሚለው ይገኝበታል። ፓርቲዎች በቁጥር መብዛታቸውን በመግለጽም መስማማት የሚችሉት እየተዋሐዱ ለመጭው ምርጫ ጠንካራ ተፎካካሪ እንዲሆኑ ሲመክሩም ነበር።