የኢፌዴሪ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ኅዳር 20/2011 ባካሔደው 9ኛ መደበኛ ስብሰባው የእርቀ ሠላም እና የአስተዳደር ወሰን እና የማንነት ጉዳዮች ኮሚሽን ለማቋቋም የቀረቡ ረቂቅ አዋጆችን ለሚመለከታቸው ቋሚ ኮሚቴዎች መርቷል።
የብሔራዊ እርቀ ሠላም ኮሚሽን በተለያዩ ማኅበራዊ እና ፖለቲካዊ ግጭቶች ምከንያት በሕዝቦች መካከል የተፈጠሩ ቁርሾዎችን ለማከም እና እርቅን ለማውረድ የሚያግዝ መሆኑ የተገለጸ ሲሆን ለውጭ ሠላምና ደኅንነት እና በተበባሪነት ለሕግ፣ ፍትሕና ዴሞክራሲ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴዎች ለዝርዝር ዕይታ መርቷል።
በተመሳሳይ የአስተዳደር፣ ወሰን እና የማንነት ጉዳዮች ኮሚሽን ለማቋቋም የቀረበው ረቂቅ አዋጅ ዙሪያ ምክር ቤቱ ውይይት ያደረገ ሲሆን ከማንነት ጋር በተያያዘ የሚነሱ ጉዳችዮን የፌዴሬሽን ም/ቤት እንዲመለከት በሕገ መንግሥቱ ሥልጣን ተሰጥቶት ሳለ አዲስ ኮሚሽን ማቋቋም ለምን አስፈለገ? የሚሉ ጥቄዎች በም/ቤቱ አባላት ተነስተዋል። ይህ ሥልጣን እና ኃላፊነት ከፌዴሬሽ ምክር ቤት በተጨማሪ አሁን በሠላም ሚኒስቴር ሥር ለተጠቃለለው የፌዴራል እና አርብቶ አደር ልማት ጉዳዮች ሚኒስቴር ተሰጥቶ እንደነበር አይዘነጋም። የማንነትና የአስተዳደር ወሰን ጉዳዮች ኮሚሽን በክልሎች የአስተዳደር ወሰንና በማንነት ጥያቄዎች ዙሪያ ለሚነሱ ችግሮች ዘላቂ መፍትሔ ለመስጠት የሚቋቋም ነው ተብሏል።
በመጨረሻም ምክር ቤቱ የአስተዳደር ወሰን እና የማንነት ጉዳዮች ኮሚሽን ለማቋቋም የቀረበውን ረቂቅ አዋጅ በዋናነት ለውጭ ግንኙንና ሠላም ጉዳዮች እና በተባባሪነት ለሕግ፣ ፍትሕና ዴሞክራሲ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴዎች ለዝርዝር ዕይታ በ4 ተቃውሞ በ1 ድምፀ ተዓቅቦ በአብላጫ ድምፅ መርቷል።
በተጨማሪም ምክር ቤቱ የፌደራል መንግሥት አስፈፃሚ አካላትን ሥልጣንና ተግባር ለመወሰን የወጣውን አዋጅ ቁጥር 1097/2011 ለማሻሻልና ለማጠቃለል የቀረበ ረቂቅ አዋጅ ላይ የተወያየ ሲሆን አዋጁን ማሻሻል ያስፈለገበት ምክንያት አዋጁ ከፀደቀ በኋላ ከተለያዩ አስፈፃሚ አካላት በቀረቡ ጥያቄዎችና በአዋጁ በተደረገው ምልክታ አብዛኛው ከቴክኒክ ችግሮች ያሉባቸው እና የይዘት ለውጥ የሚያስፈልጋቸው የአዋጁ ክፍሎች መኖራቸው ስለታመነ መሆኑን ምክር ቤቱ አስታውቋል። በመጨረሻም ረቂቅ አዋጁ ለዝርዝርዕይታ ለሕግ፣ ፍትሕና ዴሞክራሲ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ተመርቷል።
ቅጽ 1 ቁጥር 3 ኅዳር 22 ቀን 2011