በቀድሞ የሜቴክ፣ የብሔራዊ መረጃ እና ደኅንነት ኤጀንሲ፣ በፌደራል ፖሊስ እና በማረሚያ ቤት ከፍተኛ ኃላፊዎች ላይ የተከፈቱ የምርመራ መዝገቦች ላይ ፖሊስ ተጨማሪ የ14 ቀን የምርመራ ጊዜን በተደጋጋሚ እየጠየቀ፤ ፍርድ ቤቱም የተጠየቀውን ጊዜ በሙሉ ወይም በከፊል እየፈቀደ ቆይተዋል። በዚህ ሳምንትም የፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት አስረኛ ወንጀል ችሎት በያሬድ ዘሪሁን፣ በተስፋዬ ኡርጊ፣ በጄኔራል ክንፈ ዳኘው እና ኢሳያስ ዳኘው ላይ ለፖሊስ 14 የምርመራ ቀናት ፈቅዷል፡፡ ከዚህ ጋር በተያያዘ በተለይም ፖሊስ የሚጠይቀው 14 ቀን ላይ ብዙ ሲባል ከርሟል፡፡ እንደተለመደውም በማኅበራዊ መገናኛ አውታሮች ጉዳዩ የቀልድ እና የቁም ነገር ምንጭ ሆኖ ሰንብቷል፡፡ ‹‹አጣርተን እናስራለን እንጂ አስረን አናጣርም የተባለው የት ገባ›› ከሚሉ አስተያየቶች ጀምሮ ‹‹[የወንጀሉ ውስብስብነት] አይደለም 14 ቀን ይቅርና 14 አመትም የሚበቃው አይመስልም… በተገኘው መረጃ የሚፈረድበት ተፈርዶበት፣ የሚለቀቀው ተለቆ፣ ይቅር የሚባለው ይቅር ተብሎ ወደ ቀጣይ ምዕራፍ ብንሸጋገር ይበጃል›› የሚሉ ቀልዶች ተሰምተዋል፡፡ የሚከተለው ቀልድ ግን የብዙዎችን ቀልብ ስቧል፡ ‹‹ተጨማሪ የምርመራ 14 ቀን ለመጠየቅ [ፖሊሱም]፣ እስረኛውም፣ ጠበቃውም፣ ዳኛውም ተንጋግተው ፍርድ ቤት ድረስ ለምን እንደሚሄዱ ግራ ነው የሚገባኝ… አይደዋወሉም እንዴ?››
ቅጽ 1 ቁጥር 4 ኅዳር 29 ቀን 2011