ዓለም ዐቀፉን የሰብኣዊ መብቶች ቀን በማስመልከት ትኩረቱን በኢትዮጵያ ላይ ያደረገው ‹የኢትዮጵያ ሂውማን ራይትስ ፕሮጀክት› የሰብኣዊ መብቶች ጥሰት የደረሰባቸውን ሰዎች ታሪክ የሚናገር “ዝግ ደጃፎች፣ የታፈኑ ድምፆች” በሚል መሪ ቃል የፎቶ ዓውደ ርዕይ በዩጋንዳ፣ ካምፓላ ታኅሣሥ 2 እና 3 እንደሚዘጋጅ አስታወቀ።
ዓለም ዐቀፉን የሰብኣዊ መብቶች ቀን በማስመልከት የሚዘጋጀው የፎቶ ዓውደ ርዕይ ‹ሲቪል ራይት ዲፌንደር› በተባለ የስዊድን ድርጅት የገንዘብ ድጋፍ እና ኪዌታ ከሚባል የዩጋንዳ አጋራቸው ጋር በተባባሪነት የተዘጋጀ ነው። ዝግጅቱ ስድስት ወር የፈጀ ሲሆን ከኢትዮጵያ በኩል የ15 ግለሰቦች ታሪክ ከአጭር ማብራሪያ ጋር በፎቶ የሚቀርብ ይሆናል።
“የተዘጉ ደጆች፣ የታፈኑ ድምፆች” በሚል ርዕስ የሚቀርበው የፎቶ አውደ ርዕይ ትኩረቱን ዝግ ተቋማት በሚባሉት እንደ ማረሚያ ቤት እና የአእምሮ ሕሙማን ማቆያዎች ባሉ ተቋማት ውስጥ የሚፈፀሙ የሰብኣዊ መብቶች ጥሰቶች ላይ ያደረገ ሲሆን፥ የዓውደ ርዕዩ አስተባባሪዎች ተመሳሳይ ዝግጅቶችን በአገር ውስጥ የማዘጋጀት ሐሳብ እንዳላቸው ለአዲስ ማለዳ ተናግረዋል።
ቅጽ 1 ቁጥር 4 ኅዳር 29 ቀን 2011