የኢትዮጵያ አየር መንገድ ለስምንት ዓመት የቆመውን የጋና አየር መንገድ ለማስተዳደርና ድጋሚ ሥራ ለማስጀመር ተስማማ። ሥምምነቱን የጋና አቬሽን ሚኒስትር የሆኑት ጆሴፍ አዳና እና የኢትዮጵያ አየር መንገድ ሥራ አስፈፃሚ ተወልደ ገብረማርያም ተፈራርመዋል።
ጋና በድጋሚ በሚመሠረተው አየር መንገድ ላይ ከ10 በመቶ ያልበለጠ ድርሻና ሁለት የቦርድ አባላቶች ይኖሩታል ተብሏል። የጋና መንግሥትም በኢትዮጵያ አየር መንገድ የበላይነት በሚመራውና በሚተዳደረው አየር መንገድ ጉዳይ ውስጥ እጄን አልከትም ብሏል።
የጋና መንግሥት ከዚህ ቀደም እስከ 1997 ድረስ ብሔራዊ አየር መንገዱን በተሳካ መንገድ ለመምራት ቢሞክርም አሜሪካ ውስጥ እንዳይበር ከመልከሉና ሌሎች ችግሮች ጋር ተያይዞ ለማቋረጥ ተገዶ ነበር። ከዚያም ከስምንት ዓመታት በኋላ ድጋሚ ቢጀምርም ጉዞው ከአምስት ዓመት ሊዘል አልቻለም።
በአፍሪካ በትርፋማነቱና በውጤታማነቱ ታዋቂ የሆነው የኢትዮጵያ አየር መንገድ ከዚህ ቀደም የቻድ፣ ዛምቢያ እና ሞዛምቢክ አየር መንገዶችን ለማስተዳደር መሥማማቱና ድርሻ መግዛቱ አይዘነጋም።
ቅጽ 1 ቁጥር 4 ኅዳር 29 ቀን 2011