የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ሐሙስ፣ ታኅሣሥ 11/2011 ረፋድ ስብሰባው የኢትዮጵያን የመከላከያ ሠራዊት አዋጅ ማሻሻያ ረቂቅ አዋጅ አጽድቋል።
የውጭ ግንኙነትና የሠላም ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ በረቂቁ ላይ ያቀረበውን ሪፖርት ያደመጠው ምክር ቤቱ በአንድ ድምፅ ተዓቅቦ እና በአብላጫ ድምጽ አጽድቆታል፡፡
ከዚህ ቀደም የነበሩ ከ28 በላይ አንቀጾች እንደተሸሻሉ የተነገረ ሲሆን የባሕር ኃይል እንዲሁም እንደ አስፈላጊነቱ የስፔስና የሳይበር ኃይሎችን መገንባት እንዲችል የሚፈቅድ ማድረጉ ይጠቀሳል፡፡
ከሠራዊቱ አባላት ብቻ የነበረውን የመኮንኖች ምልመላ በማሻሻልም ምልመላው ሲቪሎችንም እንዲያካትት እንዲሁም፤ አዳዲስ ምልምሎች በሞራል ተቋሙን እንዲቀላቀሉ በሚልም አዳዲስ የማበረታቻ ሥርዓት እንዲዘረጋ ፈቅዷል፡፡
የሠራዊት ምልመላ፣ ቅጥርና አደረጃጀት ግልጽነት ያለውና የብሔር፣ ብሔረሰቦችና ሕዝቦችን ሚዛናዊ ተዋፅዖ ያካተተ እና ከፖለቲካ ወገናዊነት ነጻ ሆኖ እንዲደራጅም ያሳስባል፡፡
ቅጽ 1 ቁጥር 6 ታኅሣሥ 13 ቀን 2011