በደራሲ ሙሉጌታ አረጋዊ የተፃፈ ‹አብራክ› የተሰኘ መጽሐፍ ለኢትዮጵያ አንባብያን ዓርብ፣ ታኅሣሥ 5 ቀርቧል። የመጽሐፉ ዘውግ ልብ ወለድ ሲሆን በወጣቶች የፍቅር ሕይወት ታሪክ ላይ የሚያጠነጥን ሆኖ በዋናነት በኢትዮጵያ ውስጥ ስላለው ‘ጠርዝ’ እየረገጠ ስለመጣው ብሔርተኝነት ወጣቶችን ለማስተማር እንደጻፉት ደራሲው ለአዲስ ማለዳ አስታውቀዋል።
በመጽሐፉ ዙሪያ በቅርቡ የአዲስ አባባ ዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች እንዲወያዩበት ዝግጅት እየተደረገ ሲሆን በኢትዮጵያ ውስጥ በሚገኙ ሌሎች ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ውስጥም ተመሳሳይ ዝግጅት እንደሚኖር ደራሲው ጨምረው ገልፀዋል። በተጨማሪም የመጽሐፉን ሐሳብ ተደራሽነት ለማስፋት በማሰብ ወደ ፊልም ተለውጦ ለተደራሲያን በሚቀርብበት አማራጭ ዙሪያ ከባለሙያዎች ጋር እየተነጋገሩ መሆኑን ሙሉጌታ ገልፀዋል።
መጽሐፉ በ453 ገፆች ተቀንብቦ በ220 ብር ለገበያ የቀረበ ይሁን እንጂ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ስድስት ኪሎ በሚገኘው ‹ካምፓስ› ለተማሪዎች 120 ብር እንዲቀርብ መደረጉን አዲስ ማለዳ አረጋግጣለች። ‹አብራክ› ለመጀመሪያ ጊዜ የታተመው ነሃሴ 2010 በአሜሪካ አገር መሆኑ ታውቋል።
ቅጽ 1 ቁጥር 7 ታኅሣሥ 20 ቀን 2011