የጉሙሩክ ኮሚሽን የኢትዮጵያንና ኤርትራን ምጣኔ ሀብታዊ ግንኙነት ለማጠናከር ያግዛሉ ያላቸውን ኹለት ቢሮዎች በምፅዋና አሰብ እንደሚከፍት አሳውቋል።
በተያያዘ የኹለቱ አገራት ግንኙነት ወደ ሰላም በመመለሱ የንግድ እንቅስቀሴው ቢያንሰራራም በተለይም በዛላንበሳ ድንበር በኩል የተጀመረው የንግድ እንቅስቀሴ የጉምሩክ አሰራርንና ሌሎች ሕጋዊ ሥርዓቶች ስላልተበጁለት ድንበሩ እንዲዘጋ መደረጉ ይታወሳል።
የኢዜአ ዘገባ እንዳመለከተው አሁን ላይ ሕጋዊ የድንበር ንግድ እንቅስቀሴን ለማስጀመርና ለመቆጣጠር አራት የንግድ ማስተላለፊያ ኬላዎች እንዲከፈቱ ዝግጅት ተደርጓል። ከአራቱ የትራንዚት ኬላዎች ውስጥ ራማና ዛላምበሳ ይጠቀሳሉ።
ኮሚሽኑ የንግድ ማስተላለፊያ (ትራንዚት) ፕሮቶኮል ያዘጋጀ ሲሆን በቅርቡ በአገራቱ ፀድቆ ሥራ ላይ እንደሚውል ይጠበቃል።
አራቱ ኬላዎች ጊዜያዊ ናቸው የተባለ ሲሆን፣ የንግዱን እንቅስቃሴ ስፋትና ሕገ ወጥነትን ለመቆጣጠር ሲባል ተጨማሪ ኬላዎች እንደሚከፈቱም ተነግሯል።
ቅጽ 1 ቁጥር 10 ጥር 11 ቀን 2011