በኢትዮጵያ በጤና ተቋም መውለድ ከነበረባቸው እናቶች 40 በመቶዎቹ ከጤና ተቋማት ውጪ መውለዳቸውን ጤና ሚኒስቴር ገለጸ።
ሚንስትሩ ዶክተር አሚር አማን ማክሰኞ፣ ጥር 14 ለተወካዮች ምክር ቤት የመስሪያ ቤታቸውን የስድስት ወራት አፈፃፀም ባቀረቡበት ወቅት ነው፤ ይህን የተናገሩት።
ሚንስትሩ እንዳሉት በሰለጠነ ባለሙያ የሚሰጥን የወሊድ አገልግሎት ማግኘት ይጠበቅባቸው ከነበሩት አንድ ነጥብ አራት ሚሊዮን ነፍሰ ጡር እናቶች መካከል በጤና ተቋማት የወለዱት 800 ሺህዎቹ (60 በመቶ) ናቸው። ይህም 600 ሺህ (40 በመቶዎቹ) አገልግሎቱን አላገኙም ማለት ነው።
ከአምናው ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር በጤና ተቋማት የሚወልዱ እናቶች ቁጥር በአንድ በመቶ ቀንሷል። ስለዚህ ጉዳይ ከምክር ቤቱ ጥያቄ የቀረበላቸው ዶክተር አሚር የመረጃ ቋት ስርዓታቸውን እየቀየሩ መሆኑን ተከትሎ ትክክለኛ መረጃ ላይመዘገብ ይችላል ብለው እንደሚያስቡ አንስተዋል። በመረጃው ላይ የተካተተው አኃዝ የአምስት ወር መሆኑም ቁጥሩ ዝቅ እንዲል ምክንያት ይሆናል ብለዋል። ክልሎችም ትክክለኛ መረጃ እያቀበሉ እንዳልሆነ በመግለጽ ኮንነዋል።
ቅጽ 1 ቁጥር 11 ጥር 18 ቀን 2011